በአዲስ አበባ በቅርቡ ሰው አልባ ስማርት የፖሊስ ማዕከላት ተገንብተው ወደ ሥራ እንደሚገቡ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጄነራል ደመላሽ ገብረሚካኤል ገለጹ።
ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረሚካኤል ወቅታዊ ጉዳዮችን በማስመልከት ለመገናኛ ብዙሃን ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በማብራሪያቸውም ፌደራል ፖሊስ ዘመኑን የዋጀ ቴክኖሎጂ በመጠቀም የወንጀል መከላከልና ምርመራ ስራን በውጤታማነት እያከናወነ ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ የዜጎች መተግበሪያ/EFP/ ከዓለም የፖሊስ መተግበሪያዎች ጋር ተወዳድሮ በአንደኝነት እውቅና ማግኘቱን አንስተዋል።
መተግበሪያውን በቀላሉ ከፕሌይ ስቶር እና አፕ ስቶር ላይ ማውረድ የሚቻል መሆኑን ገልጸው በከፍተኛ ደረጃ የፖሊስን ስራ የሚያግዝ መሆኑን ጠቁመዋል።
ፖሊስ ህብረተሰብ አቀፍ እና መረጃ መር የወንጀል መከላከልን ተግባራዊ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰው፥ በርካታ ወንጀለኞች፣ የኮንትሮባንድ እቃዎች፣ አደገኛ እጾችና አዘዋዋሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ገልጸዋል።
የረቀቁ የወንጀል ጉዳዮችን በምርመራ የማውጣት ብቃት መገንባቱን ጠቅሰው፥ በዚህ ዓመት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የተመረቀው የፎረንሲክ ምርመራ የልህቀት ማዕከል ከፍተኛ አቅም መፍጠሩን ተናግረዋል።
አሸባሪዎች በየትኛውም ቴክኖሎጂ የሚያደርጉትን የመረጃ ልውውጥና ከመሳሪያቸው ሙሉ ለሙሉ የሰረዟቸውን መረጃዎች ጭምር አንጥሮ ማውጣት የሚያስችል ቴክኖሎጂን ታጥቀናል ነው ያሉት።
ቴክኖሎጂው በአንድ ጊዜ ከ140 መተግበሪያዎች ላይ መረጃዎችን ተንትኖ ሪፖርት የሚያቀርብ መሆኑንም ነው ኮሚሽነር ጀነራሉ የተናገሩት።
ኮሚሽነር ጀነራሉ አክለውም ፖሊስ በአዲስ አበባ በቅርቡ ሰው አልባ የፖሊስ ማዕከላትን ገንብቶ ወደ ስራ የማስገባት ዕቅድ እንዳለውም ይፋ አድርገዋል።
ይህም በአፍሪካ የመጀመሪያው እንዲሁም በዓለም አራተኛው መሆኑን ተናግረዋል።
ስማርት የፖሊስ ማዕከላቱ ማንኛውም የህብረተሰብ ክፍል የፖሊስ አመራሮችን በዲጂታል አማራጭ በቀጥታ በማግኘት ጉዳዩን የሚያስረዳባቸው ናቸው ብለዋል።
የትኛውም ግለሰብ የወንጀል ጥቆማውን ያለ ፖሊስ አባል እርዳታና ከሰው ጣልቃ ገብነት ነጻ በሆነ መንገድ በቀጥታ እንዲያቀርብ የሚያስችሉ መሆናቸውንም ገልጸዋል።
የፌደራል ፖሊስ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቱ ከፍ ማለቱን ገልጸው ይህንንም የተለያዩ ሀገራት እየመሰከሩ መሆናቸውን አመላክተዋል።
ወንጀልን ለመከላከል እና ህብረተሰቡን ከወንጀል ስጋት ነጻ እንዲሆን እየተከናወነ ያለው ስራ ተጨባጭ ውጤት እየታየበት መሆኑንም ጨምረው አንስተዋል።
ኢዜአ